
ባሕር ዳር: ነሐሴ 10/2016 ዓ.ም (አሚኮ)በምክትል ርእሰ መሥተዳድር ማዕረግ የአሥተዳደር ዘርፍ አሥተባባሪ እና የሰላም እና ፀጥታ ቢሮ ኀላፊ ደሳለኝ ጣሰው በወቅታዊ የፀጥታ ጉዳይ ዙሪያ ማብራሪያ ሰጥተዋል።
አቶ ደሳለኝ ጣሰው በችግር ውስጥም ኾነን ሰላም እና ልማትን ማረጋገጥ እንደምንችል ያልተረዱ፣ የመጣውን የሰላም ተስፋ መጠቀም የተሳናቸው ግለሰቦች ባሕር ዳር አካባቢ ሰላም እንዲደፈርስ በተለያየ የማኅበራዊ ሚዲያ በመጠቀም እንቅስቃሴ እንዲስተጓጎል እየሠሩ ነው ብለዋል።
የሚደረገው ቅስቀሳ ማንንም አይጠቅምም ያሉት አቶ ደሳለኝ ሰላም ሲኖር ልማት፣ ዕድገት እና ማኅበራዊ እንቅስቃሴ እንደሚኖር ማኅበረሰቡ ተረድቶ ቅስቀሳ የሚያደርጉ አካላትን ከመስማት እንዲቆጠብ አሳስበዋል፡፡
እነዚህ አካላት በሰላም መደፍረስ እና በሰው ደም የሚነግዱ በመኾናቸው ሰላም ወዳዱ ማኅበረሰብ ለሰላም እንዲቆምም ነው ያስገነዘቡት።
ሰላምን ማምጣት የፀጥታ መዋቅሩ ጉዳይ ብቻ ስላልኾነ በባሕር ዳር እና አካባቢው የሚደረገው ቅስቀሳ የባሕር ዳርን እና የክልሉን እጣ ፈንታ የሚያጨልም በመኾኑ ኅብረተሰቡ ከፀጥታ መዋቅሩ ጋር በመኾን ሰላሙን እንዲያስጠብቅ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
አቶ ደሳለኝ ጣሰው “የፀጥታ መዋቅሩ በአስተማማኝ ቁመና ላይ ስለሚገኝ ባሕር ዳር ላይ የሚፈጠር ነገር አይኖርም” ብለዋል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!