
ባሕር ዳር: ነሐሴ 09/2016 ዓ.ም (አሚኮ) ቻይና ለ200 ኢትዮጵያውያን ተማሪዎች ነጻ የትምህርት ዕድል መስጠቷን አስታውቃለች፡፡ የቻይና መንግሥት ለኢትዮጵያውያን ተማሪዎች ባመቻቸው ነጻ የትምህርት ዕድል ተጠቃሚ ከኾኑ 200 ተማሪዎች ውስጥ ለ23 ተማሪዎች በኢትዮጵያ የቻይና ኤምባሲ የሽኝት መርሐ ግብር ተካሂዷል።
በተለያዩ የትምህርት ዘርፎች በማስተርስ እና ፒኤችዲ ፕሮግራሞች ነው የትምህርት ዕድሉ ተጠቃሚ የኾኑት። በኢትዮጵያ የቻይና ኤምባሲ አማካሪ ሚኒስትር ሸን ኪንሚን ቻይና በተለያዩ ዘርፎች ከኢትዮጵያ ጋር በትብብር እየሠራች እንደኾነ ገልጸዋል፡፡ በትምህርት ዘርፉ ቻይና በየዓመቱ ለበርካታ ኢትዮጵያውያን ተማሪዎች ነጻ የትምህርት ዕድል እየሰጠች መኾኑን አስታውሰዋል፡፡
በዚህ ዓመትም በተለያዩ ፕሮግራሞች 200 ተማሪዎች የነጻ ትምህርት ዕድሉ ተጠቃሚ እንደሚኾኑ ነው የገለጹት፡፡ የትምህርት ሚኒስቴር የከፍተኛ ትምህርት ዓለም አቀፋዊነት እና ስኮላርሽፕ ዴስክ ኀላፊ ኢዶሳ ተርፋሳ (ዶ.ር) ተማሪዎቹ በቻይና ቆይታቸው በሚያገኙት ዕውቀት የኢትዮጵያን ቴክኖሎጂ ሽግግር እንደሚያሳድጉ ያላቸውን ዕምነት መግለጻቸውን ከትምህርት ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!