
በኢትዮጵያ ባለፉት 24 ሰዓታት የላቦራቶሪ ምርመራ ከተደረገላቸው 264 ሰዎች ውስጥ 8 ሰዎች በኮሮና ቫይረስ መያዛቸው ተረጋገጠ።
በቫይረሱ ከተያዙት ሰዎች መካከል አንድ የዘጠኝ ወር ሕጻንና እናቱ ቫይረሱ ተገኝቶባቸዋል።
የጤና ሚኒስትሯ ዶክተር ሊያ ታደሰ ለኢዜአ እንደተናገሩት በ24 ሰዓታት ውስጥ ምርመራ ከተደረገላቸው ሰዎች መካካል አንዱ ኤርትራዊ ሲሆን ቀሪዎቹ ሁሉም ኢትዮጵያውያን ናቸው።
ይህም በኢትዮጵያ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን ቁጥር 52 አድርሶታል ነው ያሉት ሚንስትሯ።
በበሽታው መያዛቸው ከተረጋገጠ ስምንቱ ሰዎች መካከል አምስቱ ከዱባይ የመጡና በለይቶ ማቆያ ውስጥ ክትትል ሲደረግላቸው የነበሩ ናቸው።
ከእነዚህም ውስጥ አንድ የዘጠኝ ወር ሕጻንና ወላጅ እናቱ ይገኙበታል።
አንድ የ25 ዓመት ሴት ኢትዮጵያዊት ከታይላንድ መጥታ በለይቶ ማቆያ ክትትል ስታደርግ የነበረች ሲሆን አንድ የ19 ዓመት ኢትዮጵያዊ የውጭ አገር ጉዞ ታሪክ የሌለው ሲሆን የንክኪ ሁኔታውም በመጣራት ላይ ይገኛል ብለዋል።
ወጣቱ በቫይረሱ ከተያዘ ሰው ጋር ንክኪ እንዳለው ተጠርጥሮ በለይቶ ማቆያ የነበረ ነው።
ሌላኛዋ የ30 ዓመት ሴት ኤርትራዊት ስትሆን ከእንግሊዝ ለንደን መጥታ በአዲስ አበባ በለይቶ ማቆያ ክትትል እያደረገች የምትገኝ ናት።
በአዲስ አበባ እና በሌሎች የክልል ከተሞች የኮሮና ቫይረስ የላቦራቶሪ ምርመራ አቅም እየጨመረ መጣቱንም ገልጸዋል።
በኢትዮጵያ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች መካከል አንድ ግለሰብ በጽኑ ሕሙማን ማቆያ ይገኛሉ።
አራቱ ያገገሙ ሲሆን ሁለቱ በቫይረሱ ምክንያት ሕይወታቸው ማለፉ ይታወሳል።
ሌላ ሁለት ግለሰቦች ደግሞ ወደ ሀገራቸው ተሸኝተዋል።