
ባሕር ዳር: ነሐሴ 02/2016 ዓ.ም (አሚኮ) “የ2016 በጀት ዓመት የኢትዮጵያን ዕድገት ያስቀጠልንበት ዓመት ነው” ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገልጸዋል። ተጠሪነታቸው ለጠቅላይ ሚኒስትሩ የኾኑ አስፈጻሚ ተቋማት የ2016 በጀት ዓመት አፈጻጸም እና የ2017 ዕቅድ የግምገማ መድረክ እየተካሄደ ነው።
በመድረኩ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመሥገን ጥሩነህ የተጠናቀቀው በጀት ዓመት በብዙ መልኩ ስኬት የተመዘገበበት ነበር ብለዋል። በዚህም የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ዕድገት ማስቀጠል ተችሏል ነው ያሉት። ለሰላም የተሰጠው ትኩረትም ለልማት ሥራዎች ምቹ ኹኔታ መፍጠሩን ገልጸው አሁንም ቀሪ ሥራ ይጠይቃል ብለዋል።
መንግሥት በ2017 በጀት ዓመት መግቢያ ወደ ተሟላ ማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ትግበራ መግባቱ ትልቅ ርምጃ እንደኾነም ገልጸዋል። ከዚህ አኳያ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ተጠሪ የኾኑ ተቋማት ለማሻሻያው ትግበራ ስኬት በምሳሌነት የሚወሰዱ ተግባራትን እንዲያከናውኑም አሳስበዋል። እንደ ኢዜአ ዘገባ በመድረኩ ተጠሪ ተቋማት የአፈጻጸም እና የዕቅድ ሪፖርታቸውን በማቅረብ ላይ ናቸው።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!