
ባሕር ዳር: ሐምሌ 30/2016 ዓ.ም (አሚኮ) ከዚህ በፊት በደላሎች የሚፈጠር እንግልት እና ያለአግባብ የሚደረግባቸውን የዋጋ ጭማሪ ማስቀረት የቻለ የታሪፍ ትኬት አገልግሎት እየተሰጠ መኾኑን በዞናል መናኸሪያው አሚኮ ያነጋገራቸው ተገልጋዮች ገልጸዋል። አገልግሎቱን ወደ ሌሎች አካባቢዎችም እንዲሰፋ ቢደረግ የበለጠ ተጠቃሚ ማድረግ እንደሚቻልም ተገልጋዮቹ ተናግረዋል።
አሽከርካሪዎችም ዘመናዊ የትኬት መቁረጫ ሥርዓት ተግባራዊ መደረጉ ተራቸውን ጠብቀው ስምሪታቸውን ለማከናወን እና ከተሳፋሪ ጋር የሚያገናኝ ክፍያ ባለመኖሩ አገልግሎታቸውን እንዳቀላጠፈላቸው ገልጸዋል።
በዞናል መናኸሪያው በቴክኖሎጂ የታገዘ ለተሳፋሪዎች ትኬት የሚቆርጡ ሠራተኞች መኖራቸውን የገለጹት የሰሜን ሸዋ ዞን ትራንስፖርት መምሪያ ኀላፊ ደጀኔ በቀለ በትራንስፖርት ዘርፍ ያለውን አገልግሎት ለማስፋት እንደሚሠራ ተናግረዋል፡፡
ተግባሩን ወደ ወረዳዎች ለማስፋትም ዕቅድ የተያዘ መኾኑን ነው የትራንስፖርት መምሪያ ኀላፊው ያብራሩት።
ዘጋቢ፡- በላይ ተስፋዬ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!