በመንሸራተት አደጋ ጉዳት ለደረሰባቸው ዜጎች 60 ሚሊየን ብር የሚገመት ድጋፍ መደረጉን የመንግሥት ኮሚዩኒኬሽን አገልግሎት አስታወቀ።

30

አዲስ አበባ: ሐምሌ 20/2016 ዓ.ም (አሚኮ) የመንግሥት ኮምዩኒኬሽን አገልግሎት ሰሞኑን በጎፋ ዞን በደረሰው የመሬት መንሸራተት አደጋ እና እየተደረገ ባለው ድጋፍ ዙሪያ መግለጫ ሰጥቷል።

መግለጫውን የሰጡት የአገልግሎቱ ሚኒስትር ድኤታ ሰላማዊት ካሳ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ዛሬ አካባቢው ላይ በመገኘት ተጎጂዎችን ማጽናናታቸውን ገልጸዋል።

አደጋው ከደረሰበት ጊዜ ጀምሮ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትን ጨምሮ የተለያዩ ሀገራት ሃዘናቸውን እና አጋርነታቸውን ሲያሳዩ መቆየታቸውን የገለጹት ሚኒስትር ድኤታዋ የተባበሩት አረብ ኢሜሬት ለተጎጂዎች ድጋፍ የሚውል 75 ቶን ምግብነክ እና ሌሎች ድጋፎችን ወደ ኢትዮጵያ ዛሬ ማለዳ መላኳን ተናግረዋል።

እስካሁን ባለው መረጃ የሟቾች ቁጥር 231 ደርሷል ብለዋል ሚኒስትር ድኤታዋ በመግለጫቸው። አሁንም የነፍስ አድን ሥራው ተጠናክሮ መቀጠሉን የገለጹት ሰላማዊት ካሳ የሟቾች ቁጥር ከዚህም በላይ ሊጨምር እንደሚችል ጠቁመዋል።

በዞኑ ስጋት ያለባቸው 14 ሺህ ዜጎች ተለይተው በአራት የጊዜያዊ መልሶ ማቋቋሚያ ስፍራዎች እንዲገቡ በጥናት መለየቱም ተመላክቷል።

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከዛሬ ጀምሮ ተግባራዊ የሚኾን የሃዘን ቀን ማወጁን ያስታወሱት ሚኒስትር ድኤታዋ በሁሉም የሀገሪቱ ክፍሎች እና በውጭ ዓለማት ባሉ ኤምባሲዎች የሀገሪቱ ሰንደቅዓላማ ዝቅ ብሎ ይውለበለባል ነው ያሉት።

መንግሥት ተጎጂዎችን በዘላቂነት ለማቋቋም ብሔራዊ ግብረ ኃይል አቋቁሞ እየሠራ ነውም ተብሏል።

ዘጋቢ፦ ቤተልሄም ሰለሞን

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

Previous articleጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ እና ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው የተጎዱ ቤተሰቦችን እና ማኅበረሰቡን በአካል ለማጽናናት በስፍራው ተገኙ።
Next articleየሕዝብን ጥያቄ በማድመጥ ችግሮችን ለመፍታት መንግሥት ያሳየውን ቁርጠኝነት እንደሚደግፉ የጎንደር ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ፡፡