
ባሕር ዳር: ሐምሌ 19/2016 ዓ.ም (አሚኮ) የሩሲያንና የኢትዮጵያን የረጅም ጊዜ ግንኙነት የሚመጥን የሩሲያ ባለሃብቶች የኢንቨስትመንት ፍሰት እንዲኖር እንደሚፈልጉ የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍስሃ ይታገሱ (ዶ.ር)ገልጸዋል፡፡
ዋና ሥራ አስፈጻሚው ይህን የገለጹት የሩሲያ-አፍሪካ የኢኮኖሚ ትብብር ኮሚቴ ልዑካን ቡድን አባላት ጋር በጽሕፈት ቤት ቤታቸው ውይይት ባደረጉበት ወቅት ነው፡፡ ዶክተር ፍስሃ ከልዑካን ቡድኑ ጋር በነበራቸው ቆይታ በኮርፖሬሽኑ ስር በሚተዳደሩ ኢንዱስትሪ ፓርኮችና የድሬዳዋ ነጻ የንግድ ቀጣና ስለሚገኙ ምቹ የኢንቨስትመንት ሁኔታዎች፣ የኢንቨስትመንት ማበረታቻዎችና ለኢንቨስተሮች ዝግጁ የተደረጉ መሰረተ ልማቶች ዙሪያ ዝርዝር ገለጻ አድርገዋል፡፡
የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን በኢንዱስትሪ ፓርኮች ያለውን የኢንቨስትመንት ፍሰት ለማሳደግ ከኤምባሲዎች፣ ከዓለም አቀፍ ማህበራትና ልማት ድርጅቶች ጋር በትብብር እየሠራ እንደሚገኝ ከኮርፖሬሽኑ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!