
አዲስ አበባ: ሐምሌ 11/2016 ዓ.ም (አሚኮ)በአትክልትና ፍራፍሬ (ሆርቲካልቸር) ዘርፍ ላይ ያሉ ማነቆዎችን ለመፍታት ልዩ ትኩረት ሰጥቶ መሥራት እንደሚያስፈልግ የግብርና ሚንስቴር አሳስቧል።
የግብርና ሚኒስቴር ያዘጋጀው ብሔራዊ የሆርቲካልቸር ስትራቴጂ የምክክር አውደ ጥናት ተካሂዷል::
የግብርና ሚኒስትሩ ግርማ አመንቴ (ዶ.ር) ዘርፉ የሥርዓተ ምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ እና የውጭ ምንዛሪ ግኝትን ከማሳደግ አኳያ ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያበረከተ ይገኛል ነው ያሉት። ከአበባ፣ አትክልትና እና ፍራፍሬ ልማት በዚህ ዓመት 535 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር መገኘቱን ሚኒስትሩ ገልጸዋል::
የመሬት አቅርቦት ፣ መሠረተ ልማት፣ ፋይናንስ፣ የገበያና የዲጂታል መረጃ ሥርዓት፣ የማበረታቻ ሥርዓት እና የመልካም አሥተዳደር የዘርፉ ማነቆዎች መኾናቸው በውይይቱ ተነስቷል፡፡
በዘርፉ የተከሰቱ ችግሮችን በመቅረፍ ዙሪያ ያተኮረ ረቂቅ ሰነድ ለውይይት ቀርቦ ወደ ተግባር ለማስገባት የሚያስችሉ ውሳኔዎች እንደሚጸድቅም ከአውደ ጥናቱ ይጠበቃል።
በአውደ ጥናቱ በዘርፉ የተሰማሩ ባለሃብቶች፣ አምራቾች፣ የዘርፉ ተመራማሪዎች እና የሚመለከታቸው የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ሠራተኞች ተገኝተዋል።
ዘጋቢ፦ ደረጀ አምባው
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!