
ባሕር ዳር፡ ሐምሌ 06/2016 ዓ.ም (አሚኮ) ከሐምሌ 03 እስከ ሐምሌ 05/2016 ዓ.ም ሲሰጥ የነበረው የ12ኛ ክፍል የማኅበራዊ ሳይንስ ብሔራዊ ፈተና በስኬት መጠናቀቁን ተከትሎ በምክትል ርእሰ መሥተዳድር ማዕረግ የማኅበራዊ ዘርፍ አሥተባባሪ እና የአማራ ክልል ትምህርት ቢሮ ኅላፊ ሙሉነሽ ደሴ (ዶ.ር) በሂደቱ ለተሳተፉ አካላት ምሥጋና አቅርበዋል።
ሙሉነሽ ደሴ (ዶ.ር) “በየደረጃው ያለው የመንግሥት መዋቅር ከማኅበረሰቡ ጋር በትብብር መሥራቱ ለስኬት አብቅቶናል” ብለዋል።
በተለይም ከወጣቶች፣ ሀገር ሽማግሌዎች፣ ሃይማኖት አባቶች እና ከተማሪ ወላጆች ጋር በቅንጅት መሠራቱ ለፈተናው በስኬት መጠናቀቅ ጉልህ አስተዋጽኦ እንደነበረው ተናግረዋል።
የአማራ ክልል ትምህርት ቢሮ በማኀበራዊ ትስስር ገጹ እንዳሰፈረው ሙሉነሽ ደሴ (ዶ.ር) በጋራ ግብ ላይ መግባባት፣ በተግባቡት ልክ መትጋት እንዲሁም ትጋትን ማቀናጀት ጉዟችንን ያቃናል ብለዋል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!