
ጎንደር: ሐምሌ 03/2016 ዓ.ም (አሚኮ) የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት አስራት አፀደወይን (ዶ.ር) እንደተናገሩት ዩኒቨርሲቲው ከምዕራብ ጎንደር፣ ወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ፣ ከማዕከላዊ ጎንደር እና ከጎንደር ከተማ ሀገር አቀፍ የማጠቃለያ ፈተናውን የሚወስዱ 11 ሺህ ተማሪዎችን ሲሠራ የቆየ ሲሆን 9 ሺህ 762 የማኅበራዊ ሳይንስ ተማሪዎች በዛሬው ዕለት ፈተናውን እየወሰዱ መኾኑን አስታውቀዋል።
ዩኒቨርሲቲው ተፈታኝ ተማሪዎቹ በስኬት ይፈተኑ ዘንድ ከሚመለከታቸው ባለ ድርሻ አካላት ጋር በመተባበር የተለያዩ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች ሢሠራ መቆየቱንም ፕሬዚዳንቱ ተናግረዋል። ዶክተር አስራት ተማሪዎች በፈተናው ወቅት በራስ መተማመናቸውን አዳብረው እንዲቀርቡ የሥነ ልቦና ዝግጅት ሥልጠና በየትምህርት ቤቶቻቸው ሲወስዱ መቆየታቸውን አስታውሰው፣ ለዚህ ደግሞ የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ድርሻ ላቅ ያለ መኾኑን ተናግረዋል።
ዩኒቨርሲቲው በሁለተኛ ዙር ሀገር አቀፍ የ12ኛ ክፍል የማጠቃለያ ፈተናን የሚወስዱ 11 ሺህ የተፈጥሮ እና ቀመር ሳይንስ ተማሪዎችን ለመቀበል ከወዲሁ መዘጋጀቱንም ፕሬዚዳንቱ ተናግረዋል።
ዘጋቢ:-ቃል ኪዳን ሀይሌ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!