
ባሕር ዳር: ሰኔ 30/2016 ዓ.ም (አሚኮ) በጎንደር ከተማ ያለውን አንጻራዊ ሰላም ወደ አስተማማኝ ሰላም ለመቀየር “ሰላም ለሁሉም ሁሉም ለሰላም” በሚል መሪ መልዕክት በቀበሌ ደረጃ የሕዝብ የሰላም ኮንፈረንስ ተካሂዷል።
በኮንፈረንሱ የተሳተፉት የከተማዋ ነዋሪዎች የቱሪስት ከተማዋ ጎንደር ባለፉት ጊዜያት በተከሰተው የሰላም እጦት ምክንያት በቱሪስት ድርቅ መመታቷን ተናግረዋል።
ለቱሪስቶች ወደ ከተማዋ መምጣት ዋናው ሰላም ነው ያሉት ተሳታፊዎቹ ሰላሙ ባለመረጋገጡ ከትንሽ እስከ ትልቁ ሠርቶ የሚያድረው ሰው እንደተጎዳ አስረድተዋል።
ግጭቱ ብዙ ነገር እያሳጣቸው እንደኾነ የሚገልጹት ነዋሪዎች ለሕዝብ እና ለከተማዋ ዕድገት የሚያስብ ሁሉ ከግጭት በመውጣት ያለውን ጥያቄ በውይይት እና በንግግር እንዲፈታ ጠይቀዋል።
የጎንደር ከተማ የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን መምሪያ እንዳለው ተወያዮቹ እስካሁን ያለው ጉዳት ይበቃል፤ ወደ ልማት እና ራስንም ሀገርንም ወደ ሚጠቅም እሳቤ መመለስ ያስፈልጋል ነው ያሉት።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
