
ባሕር ዳር፡ ሰኔ 29/2016 ዓ.ም (አሚኮ) በምስራቅ ጎጃም ዞን ስናን ወረዳ አሥተዳደር በወቅታዊ የልማትና የሰላም ግንባታ ዙሪያ በወረዳው ውስጥ ከተውጣጡ የማኅበረሰብ ክፍሎች ጋር የምክክር መድረክ አካሄደዋል።
“የሰላም እጦቱ የዘመናት ጥያቄያችን የነበረዉን የልማት ጥያቄ የፌደራል መንግሥቱ መልስ የሰጠን ቢሆንም እድሉን እንዳንጠቀም አድርጎናል” ያሉት የስናን ወረዳ አሥተዳዳሪ አየነው ደለለ ሰላማችንን በማፅናት ወረዳችንን በማልማት ሕዝባችንን ተጠቃሚ ልናደርግ ይገባል ብለዋል።
መንግሥት የስናን ወረዳ ሕዝብ ከዚህ በፊት ሲጠይቃቸው የነበሩ የልማት ጥያቄዎችን ለመመለስ እየሠራ ነዉ ያሉት የስናን ወረዳ ብልፅግና ፓርቲ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ባወቀ ሞላ ሰላም የልማታችን መሰረት መሆኑን ተገንዝቦ የሰላም አማራጭ በመቀበል ሰላም እንዲሰፍን የድርሻቸዉን እንዲወጡ መልእክት አስተላልፈዋል።
“ከእርስ በእርስ መገዳደል ወጥተን ሰላምን በማስፈን ልማታችንን ለማረጋገጥ የበኩላችንን ሚና እንወጣለን” ብለዋል ተወያዮቹ።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!