
ባሕር ዳር: ሰኔ 28/2016 ዓ.ም (አሚኮ)የኮምቦልቻ ከተማ አሥተዳደር የከተማዋን ሰላም በአስተማማኝ ሁኔታ ለማስጠበቅ በየደረጃው የሚገኝ የፀጥታ መዋቅር የአቅም ግንባታ ሥልጠና እያካሄደ ነው።
የኮምቦልቻ ከተማ አሥተዳደር ሰላም እና ፀጥታ መምሪያ ኀላፊ ኮማንደር ሰይድ ዓሊ የከተማውን ሰላም ለማስጠበቅ እና የፀጥታ ኀይሉን አቅም ለመገንባት በአመለካከት፣ በሥነ ልቦና እና በተግባር ልምምድ የተጀመሩ ሥልጠናዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አብራርተዋል።
ኅብረተሰቡ የራሱን ሰላም እንዲያስጠብቅ ከብሎክ ጀምሮ የማደራጀት፣ የግንዛቤ ፈጠራ እና ለፀጥታ ኀይሉ አጋዥ እንዲኾን በተሠራው ሥራ አበረታች ውጤት ተገኝቶበታል ነው ያሉት።
በሥልጠናው የተሳተፉ የሚሊሻ አባላት በወሰዱት ሥልጠና አቅማቸውን ማሳደግ መቻላቸውን እና በቀጣይ የሚሰጣቸውን ግዳጅ በአስተማማኝ ደረጃ ለመወጣት ዝግጁ መኾናቸውን አብራርተዋል።
የኮምቦልቻ ከተማ አሥተዳደር ሚሊሻ ጽሕፈት ቤት የሰው ኀይል አደረጃጀት ፀጥታ እና ስምሪት ቡድን መሪ መስፍን ፍሰሃ ለተመረጡ የገጠር ቀበሌዎች የሚሊሻ አባላት የንድፈ ሃሳብ ሥልጠና መሰጠቱን መግለጻቸውን ከኮምቦልቻ የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን መምሪያ የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!