
ጎንደር: ሰኔ 13/2016 ዓ.ም (አሚኮ) የጎንደር ከተማ አሥተዳደር ትምህርት መምሪያ ምክትል ኅላፊ ነጻነት መንግስቴ በከተማ አሥተዳደሩ በ61 መፈተኛ ጣቢያዎች ለ6 ሺህ 84 ተማሪዎች የ6ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተናውን ለመስጠት ታስቦ እንደነበር ገልጸዋል። ይሁን እንጅ ከዚህ በፊት የነበረው የጸጥታ ችግር በፈጠረው መስተጎጎል ምክንያት በ4 ትምህርት ቤቶች 234 ተማሪዎች ለፈተና አለመቀመጣቸውን ምክትል ኅላፊው ጠቅሰዋል።
በመኾኑም በ57 መፈተኛ ጣቢያዎች 5 ሺህ 860 ተማሪዎች ፈተናቸውን እየወሰዱ ነው ብለዋል። የፈተና አሰጣጥ ሂደቱንም የከተማው ከፍተኛ የሥራ ኀላፊዎች ተዟዙረው ተመልክተዋል። ፈተናው ሰላማዊ በኾነ መንገድ እየተሠጠ መኾኑንም የጎንደር ከተማ አሥተዳደር ትምህርት መምሪያ ምክትል ኅላፊ ነጻነት መንግስቴ ተናግረዋል።
በአምስት የትምህርት ዓይነቶች የሚሠጠው ክልል አቀፍ የስድስተኛ ክፍል ፈተና ሰኔ 14/2016 ዓ.ም ይጠናቀቃል።
ዘጋቢ፦ አገኘሁ አበባው
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!