
ሰቆጣ: ሰኔ 06/2016 ዓ.ም (አሚኮ)በዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር እንሰሳት እና ዓሳ ሃብት ልማት ተጠሪ ጽሕፈት ቤት አዘጋጅነት በብሔረሰብ አስተዳደሩ የእንሰሳት ሃብት እና የሌማት ትሩፋት ተጠቃሚነት ዙርያ የንቅናቄ መድረክ እየተካሄደ ነው። በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የብሔረሰብ አስተዳደሩ ዋና አስተዳዳሪ ኃይሉ ግርማይ የሌማት ትሩፋትን በተጠናከረ እና በተጠና መንገድ በማልማት ዋግ ኽምራን ከሚያጋጥማት ተደጋጋሚ ድርቅ ማላቀቅ እንችላለን ብለዋል።
በሰቆጣ ከተማ አስተዳደር በንብ ማነብ እና በእንሰሳት እርባታ የታዩ ለውጦች አበረታች ናቸው ያሉት ዋና አስተዳዳሪው ሌሎች ወረዳዎችም የሌማት ትሩፋት ሥራን በማጠናከር እና የተሞክሮ ቅመራ ሥራ በመሥራት ለውጥ ማምጣት ይገባቸዋል ብለዋል። በመጭው የክረምት ወቅት በአትክልት እና ፍራፍሬ እንዲኹም በወተት ልማት አተኩረን ልንሠራ ይገባል ብለዋል አቶ ኃይሉ ግርማይ።
በንቅናቄ መድረኩ የ2016 በጀት ዓመት የሥራ አፈጻጸም እንደሚቀርብ እና የሌማት ትሩፋት የልምድ ልውውጥ እንደሚደረግ የወጣው መርሐ ግብር ያመላክታል።
ዘጋቢ፦ ደጀን ታምሩ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!