
ወልድያ: ሰኔ 01/2016 ዓ.ም (አሚኮ) “ኢትዮጵያ ታምርት እኛም እንሸምት” በሚል መሪ መልዕክት የሰሜን ወሎ ዞን ኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንት መምሪያ በጋሸና ከተማ የኢንቨስትመንት ፎረም እያካሄደ ነው። በጋሸና ከተማ ሥራ የጀመሩ እና ሊጀምሩ የተዘጋጁ 11 ኘሮጀክቶች መኖራቸውን የከተማዋ ከንቲባ ፀጋ ውቤ ገልጸዋል። ከተማዋ በቀን ከ3ሺህ በላይ እንግዳን የምታስተናግድ እና ለወደብ ቅርብ መኾኗ ለኢንቨስትመንት ተመራጭ ያደርጋታል ብለዋል።
የሰሜን ወሎ ዞን ኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንት መምሪያ ኀላፊ ሞላ ደሱ ዞኑ 5 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር ካፒታል ላስመዘገቡ 163 አልሚ ባለሃብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ መስጠቱን ገልጸዋል። የሰሜን ወሎ ዞን ዋና አሥተዳዳሪ አራጌ ይመር በጦርነቱ ጉዳት የደረሰበትን አልሚ ባለሃብት ማነቃቃት የፎረሙ ዓላማ ነው ብለዋል።
በሰሜኑ ጦርነት ምክንያት በ197 ኘሮጀክቶች የሚሠሩ ከ4ሺህ በላይ ወገኖች ከሥራ ውጭ ኾነዋል ያሉት ዋና አሥተዳዳሪው ኢንቨስትመንት በባሕሪው ሰላምን የሚፈልግ በመኾኑ ሁላችንም የየድርሻችንን እንወጣ ሲሉ አሳስበዋል። በፎረሙ የፌዴራል፣ የክልል እና የዞን የሥራ ኀላፊዎች ተገኝተዋል። የልማት ባንክ ተወካዮች፣ የወረዳ መሪዎች እና ባለሃብቶች የፎረሙ ተሳታፊ ናቸው። በጋሸና ከተማ ሥራ የጀመሩ እና ገና በተከላ ላይ ያሉ ኢንዱስትሪዎች ተጎብኝተዋል።
ዘጋቢ፦ ካሳሁን ኃይለሚካኤል
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
