
ባሕር ዳር: ግንቦት 30/2016 ዓ.ም (አሚኮ)የሲዳማ ክልል ርእሰ መሥተዳድር ደስታ ሌዳሞ እና የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክትል ርእሰ መሥተዳድር ተስፋየ ይገዙ በባሕር ዳር ከተማ ውስጥ የሚገነቡ መሠረተ ልማቶችን እየጎበኙ ነው። የባሕር ዳር ከተማ አሥተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው ከሌሎች የክልሉ እና የከተማ አሥተዳደሩ ከፍተኛ መሪዎች ጋር በመኾን ለሕዝብ የሚሠሩ የተለያዩ መሠረተ ልማቶችን አስጎብኝተዋል።
በጣና ሐይቅ ዳርቻ ከሚገነቡት አረንጓዴ ልማቶች መካከል የሕዳር 11 እና የዲፖ መናፈሻዎችን ተመልክተዋል። የሐይቁን ዳርቻ ተከትሎ የሚገነባው የጣና ማሪና ግዙፍ፣ ውብ እና ዘመናዊ መናፈሻም አንዱ የጉብኝታቸው መዳረሻ ነበር። መሪዎቹ በከተማዋ ውስጥ በዘመናዊነቱ እና በስፋቱ የመጀመሪያ የኾነውን የአስፋልት መንገድ ግንባታም ተመልክተዋል። መሪዎቹ ቀሪ ሥራዎቹ በቅርብ ጊዜ ተጠናቅቀው ለውድድር ክፍት ለማድረግ እየተሠራ ያለውን የባሕር ዳር ዓለም አቀፍ ስታዲየምንም ተመልክተዋል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!