“ከየትኛውም የሀገራችን አቅጣጫ የሚመጡ ጥቃቶችን ለመመከት የሚያስችል የተሟላ ወታደራዊ ቁመና ተገንብቷል” ጄኔራል አበባው ታደሰ

9

ባሕር ዳር: ግንቦት 16/2016 ዓ.ም (አሚኮ) የኮማንዶ እና አየር ወለድ ዕዝ ማሠልጠኛ ማዕከል ከዕዙ የተለያዩ ክፍሎች በመመልመል በአመራር ትምህርት ቤቱ ያሠለጠናቸውን ሁለተኛ ዙር የበታች ሹም መሪዎችን አስመርቋል። በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የጦር ኀይሎች ምክትል ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ጄኔራል አበባው ታደሰ የሀገራችንን ዕድገት የማይፈልጉ ኀይሎች በራሳቸው ያቃታቸውን ጽንፈኞችን በማሰማራት ሀገራችንን ለመበታተን መሞከራውን ገልጸዋል፡፡ ነገር ግን በጀግናው ሠራዊታችን እና በአስተዋዩ ሕዝባችን ድጋፍ ህልማቸው እንዲመክን መደረጉን ገልጸዋል።

ጄኔራል አበባው “ሀገራችንን በተለያየ አቅጣጫ ለመወጠር ሞክረው የነበሩ ኀይሎችን ስጋት ወደማይኾኑበት ደረጃ አድርሰናል” ብለዋል፡፡ ሀገራችንን ለማጽናት በተከፈለው ውድ ዋጋ የመጣውን ሰላም ለማረጋገጥ በርካታ ሥራዎች እየተሠሩ እንደሚገኙ ጄኔራል አበባው ጠቁመዋል፡፡ ከየትኛውም የሀገራችን አቅጣጫ የሚመጡ ጥቃቶችን ለመመከት የሚያስችል የተሟላ ወታደራዊ ቁመና ተገንብቶ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

ተመራቂ የበታች ሹም መሪዎችም ያገኙትን አቅም ወደየሚመደቡባቸው ቦታዎች በመተግበር ኀላፊነታቸውን ሊወጡ እንደሚገባ አሳስበዋል። በዝግጅቱ ላይ ተመራቂዎች የተለያዩ ወታደራዊ ትርዒቶችን ማሳየታቸውን ከኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ማኅበራዊ ትስስር ገጽ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

Previous article“በፓርኩ ያየነው የሥራ እንቅስቃሴ የዲጂታል 2025 ስትራቴጂን ዕውን ለማድረግ ትልቅ ተቋም እየተገነባ መኾኑን ነው” ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Next article“በመማር ማስተማሩ ዙሪያ ቀሪ ሥራዎችን በቀሪ ጊዜያት መፈጸም እና ለሚቀጥለው ዓመት ግብዓት መያዝ ይገባል” ሙሉነሽ ደሴ (ዶ.ር)