
ባሕር ዳር: ግንቦት 09/2016 ዓ.ም (አሚኮ) የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሥራ ኀላፊዎች እና አባላት የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን የሥራ እንቅስቃሴን እየጎበኙ ነው። በጉብኝቱ ዋና አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎን ጨምሮ ምክትል አፈ ጉባኤ ሎሚ በዶ፣ የምክር ቤቱ ቋሚ ኮሚቴ ሠብሣቢዎች እና አባላት ተገኝተዋል።
የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር መሐመድ እድሪስ እና የሥራ ኀላፊዎች የተቋሙን የሥራ እንቅስቃሴ በተመለከተ ገለጻ አድርገዋል። ዋና ዳይሬክተሩ “የሕዝብ መገናኛ ብዙኃን የኅብረተሰቡን ባሕል እና እሴት በማይቃረን መልኩ እንዲሠሩ በቴክኖሎጂ የታገዘ የክትትል ሥራ እየተሠራ ነው” ሲሉ ተናግረዋል።
የሀሰተኛ መረጃ እና የጥላቻ ንግግሮችን ለመከላከል ከሕዝብ የሚመጡ ቅሬታዎችን በመለየት መፍትሔ እንዲያገኙ እየተሠራ ነውም ብለዋል። ኢዜአ እንደዘገበው መገናኛ ብዙኃን ማኅበረሰብን የመቅረጽ ኀላፊነታቸውን እንዲወጡ ባለሥልጣኑ ከሥልጠና ጀምሮ የተለያዩ ድጋፎችን እያደረገ መኾኑንም አብራርተዋል። ባለሥልጣኑ የመገናኛ ብዙኃን ፍቃድን ጨምሮ ከ18 በላይ አገልግሎቶችን በኢ ሰርቪስ እየሰጠ መኾኑም ተጠቅሷል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
