በብልፅግና ፓርቲ እና በሕወሃት መካከል የተጀመረው የፓርቲ ለፓርቲ ፓለቲካዊ ውይይት ተካሄደ።

79

ባሕር ዳር: ግንቦት 07/2016 ዓ.ም (አሚኮ)በብልፅግና ፓርቲ እና በሕወሃት መካከል የተጀመረው የፓርቲ ለፓርቲ ፓለቲካዊ ውይይት ለሦስተኛ ጊዜ በመቐለ ከተማ በዛሬው ዕለት ግንቦት 7/2016 ተካሂዷል::በውይይቱም ቀደም ሲል የተደረሰውን የፓርቲ ለፓርቲ የግንኙነት መርሆዎች በማስታወስና የተጀመረውን ዋና ዋና አጀንዳዎች የመለየት ሂደት በማጠናቀቅ በአጀንዳዎቹ ቅደም ተከተል ላይ ከመከሩ በኃላ የጋራ መግባባት ላይ ደርሰዋል::

በመጀመርያ አጀንዳነት የተለየውን ዘላቂ ሰላም ማረጋገጥ ጋር ተያይዞ በዝርዝር ውይይት በማድረግ ሁለቱም ፓርቲዎች ለዘላቂ ሰላም መረጋገጥ በጋራ በቁርጠኝነት ለመሥራት በመስማማት፤ በመጨረሻም :-

1. በቅርቡ በራያ የተፈጠረውን የግጭት ክስተት በተመለከተ በዝርዝር ውይይት በማካሄድ፣ ክስተቱ መፈጠር ያልነበረበትና ከጀመርነው ዘላቂ ሰላም የማረጋገጥ ሂደት ጋር የሚቃረን እንደሆነ መግባባት ላይ ደርሰዋል::

2. ማናቸውንም ጉዳዮች በሰላማዊ መንገድና በውይይት እየፈቱ ለመሄድ ሁለቱም አካላት የበኩላቸውን ፓለቲካዊ ድርሻ ለመወጣትና በቁርጠኝነት ለመሥራት ተስማምተዋል:: በተያያዘም የሚኖሩ የኮሙኒኬሽን ሥራዎች የሰላም ሂደቱን የሚደግፉ እና ግጭት ቀስቃሽ ከሆኑ ንግግሮችና ይዘቶች የተቆጠቡ እንዲሆኑ መግባባት ላይ ደርሰዋል ::

3. ማናቸውንም ግጭት የሚፈጥሩ አዝማምያዎች በጋራ ለመከላከል እና ከተፈጠሩም በፍጥነት ለመቆጣጠር በቁርጠኝነት ለመሥራት ተስማምተዋል::

4. የፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነትን ወደ መሬት ለማውረድ እየተሠሩ ላሉ ሥራዎች ስኬት ምቹ ፓለቲካዊ ሁኔታ ለመፍጠር ሁለቱም ፓርቲዎች ኃላፊነታቸውን ለመወጣት መስማማት ላይ ደርሰዋል::

በቀጣይም በሌሎች አጀንዳዎች ላይ ለመወያየት በመስማማት የእለቱን ውይይት አጠናቅቋል::

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

Previous article“ያደገ መንግሥት ትልቁ እና የመጨረሻው ጉዳይ ዜጎችን በፍጥነት እና በታማኝነት አገልግሎት መስጠት ነው” ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመሥገን ጥሩነህ
Next articleኢትዮጵያ የዓለም የንግድ ድርጅትን የምትቀላቀልበትን ሂደት ማፋጠን በሚቻልባቸው መንገዶች ዙሪያ ውይይት ተካሄደ።