
ደብረ ብርሃን: ሚያዚያ 24/2016 ዓ.ም (አሚኮ)ጸሎተ ሐሙስ ትህትና እና ምስጢር የተገለጠባት፣ ከዐቢይ ጾም የመጨረሻው ሳምንት የሰሙነ ሕማማት ቀናት መካከል አራተኛው ዕለት ነው። በዕለቱ ጌታችን እና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የደቀ መዛሙርቱን እግር ዝቅ ብሎ በማጠብ ትህትናን አስተምሮበታል፡፡ በዚኽም ሰዎች ዝቅ ብለው ታናናሾቻቸውን መመልከት እና ማገልገል እንደሚገባቸው ትምህርት የሚሰጥበት ዕለት ነው፡፡
አሁን ላይ የጎደለን ትህትና ነው ያሉት በደብረ ብርሃን ከተማ የደብረ ገነት ቅዱስ ኡራኤል እና የአንቀጸ ምህረት ቅዱስ ሚካኤል አብያተ ክርስቲያናት አሥተዳዳሪ መላአከ ገነት ቀሲስ ኃይሌ አየለ “ልባችንን ለፍቅር እና ለትህትና ክፍት ማድረግ ይኖርብናል” ሲሉ ያስተምራሉ፡፡
ኢየሱስ ክርስቶስ እኛ በምድር ላይ ስንኖር ማድረግ ያለብንን እንድናደርግ በንድፈ ሃሳብ ማስተማር ብቻ ሳይኾን ጾም ፣ ጸሎት እና ትህትናን በተግባር ገልጾ ያሳየበት ቀን ነው ብለዋል፡፡ መልአከ ገነት ክርስትና ከስም መጠሪያነት በላይ የምንኖረው ሕይዎት በመኾኑ የምግባር ሰዎች መኾን አለብን ነው ያሉት፡፡
እንደኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስትያን ሥርዓት የጸሎተ ሐሙስ ስያሜዎችም ጸሎተ ሐሙስ፣ ሕጽበተ እግር፣ የምሥጢር ቀን፣ የሐዲስ ኪዳን እና የነጻነት ሐሙስ በመባልም ይጠራል ብለዋል፡፡
ዘጋቢ፡- በላይ ተስፋዬ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!