
ባሕር ዳር: ሚያዝያ 24/2016 ዓ.ም (አሚኮ) ሀገራዊ ጥሪውን ተቀብለው በሁለተኛው ምዕራፍ ወደ ሀገራቸው ለመጡ የሁለተኛ ትውልድ ኢትዮጵያውያን በቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ አቀባበል እየተደረገላቸው ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) በተለያዩ የዓለም ክፍሎች የሚኖሩ ሁለተኛ ትውልድ ኢትዮጵያውያንን ወደ ሀገራቸው እንዲመጡ ጥሪ ማቅረባቸው ይታወቃል።
ይህንኑ ተከትሎ ዛሬ ማለዳ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ወደ ሀገራቸው እየገቡ ነው። ኢትዮጵያውያኑ ቦሌ ዓለም ዓቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርሱ የቱሪዝም ሚኒስትር አምባሳደር ናሲሴ ጫሊ እና ሌሎች የመንግሥት የሥራ ኀላፊዎች አቀባበል አድርገውላቸዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባደረጉት ጥሪ በመጀመሪያው ምዕራፍ “ከባሕላችሁ ጋር ተዋወቁ” በሚል ሃሳብ ተመሳሳይ መርሐ ግብር መካሄዱ ይታወቃል። ሁለተኛው ምዕራፍ “ከታሪካችሁ ተዋወቁ” በሚል መሪ ሃሳብ ነው እየተካሄደ ያለው። በቀጣይ የሚካሔደው ሦስተኛው ምዕራፍ “አሻራችሁን አኑሩ” በሚል ከሰኔ 2016 ዓ.ም እስከ መስከረም 20/2017 ዓ.ም ድረስ እንደሚከናወን ኢዜአ ዘግቧል፡፡
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!