
አዲስ አበባ: ሚያዚያ 22/2016 ዓ.ም (አሚኮ) የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ተቋሙ ከተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት የተወጣጡ ዲፕሎማቶችን እያሠለጠነ ይገኛል። አካዳሚው ለኢትዮጵያ እና ለአፍሪካ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያላቸው መሪዎችን የማፍራት ግብን አንግቦ እየሠራ ያለ መንግሥታዊ ተቋም ነዉ።
ተቋሙ ከተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት ለተወጣጡ ዲፕሎማቶች ሥልጠና እየሰጠ ሲኾን በሁለት ወር ጊዜ ውስጥም ለ120 የአፍሪካ ዲፕሎማቶች ሥልጠና መሥጠቱን የተቋሙ ፕሬዚዳንት ዛዲግ አብርሃ ገልጸዋል። “ኢትዮጵያ አፍሪካዊያን የለውጥ አራማጆችን የማብቃት ሥራ አጠናክራ ትቀጥላለች” ሲሉም ተናግረዋል።
አቶ ዛዲግ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዲፕሎማቶችን ማሠልጠኗ በዲፕሎማሲዉ ዘርፍ ተጽዕኖ ፈጣሪነቷ እንዲጨምር ያደርጋል፤ የአፍሪካውያን ወንድማማችነትን ያጎለብታል፤ የአፍሪካን ውህደትም ያፋጥናል ብለዋል። በርካታ የአፍሪካ ሀገራትም የኢትዮጵያን ተነሳሽነት እንደሚያደንቁ እና አብረዉ መሥራት እንደሚፈልጉ መግለጻቸዉን ፕሬዚዳንቱ ገልጸዋል።
ዘጋቢ፡- በለጠ ታረቀኝ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
