
እንጅባራ: ሚያዚያ 21/2016 ዓ.ም (አሚኮ) በብሔረሰብ አሥተዳደሩ የ9 ወራት ወቅታዊ የፀጥታ እና የልማት ሥራዎች አፈጻጸም ግምገማ በእንጅባራ ከተማ ተካሂዷል። የአዊ ብሔረሰብ አሥተዳደር ዋና አሥተዳዳሪ ቴዎድሮስ እንዳለው ባለፉት 9 ወራት የተፈጠረውን የሰላም መደፍረስ ተከትሎ የጠላት እንቅስቃሴን ታሳቢ ያደረገ የሕዝብ ንቅናቄ በመፍጠር ሊደርስ የሚችለውን ቀውስ መቀነስ መቻሉን ተናግረዋል።
ከገባንበት ቀውስ ለመውጣት ብቸኛው መፍትሔ ሕዝባዊ አንድነትን ማፅናት ነው ያሉት ዋና አሥተዳዳሪው ኅብረተሰቡ ከከፋፋይ አጀንዳዎች በመራቅ ለሰላም ዘብ ሊቆም እንደሚገባም አስገንዝበዋል ። በግጭቱ ምክንያት የተፈናቀሉ ወገኖችን ወደ ቀያቸው በመመለስ የክረምት የእርሻ ሥራዎችን እንዲሠሩ ማድረግ ጊዜ የማይሰጠው ጉዳይ እንደኾነም ጠቁመዋል።
የግምገማው ተሳታፊዎችም የሰላም ሁኔታው መሻሻል በታየባቸው አከባቢዎች የመንግሥት መደበኛ ሥራዎችን ለማስቀጠል ጥረት እያደረጉ መኾናቸውን አንስተዋል። የተጠናከረ የሕግ ማስከበር ሥራ በመሥራት ኅብረተሰቡን ከተራዘመ ስቃይ ማላቀቅ እንደሚገባም ተሳታፊዎች አንስተዋል፡፡
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!