
ባሕር ዳር: ሚያዚያ 14/2016 ዓ.ም (አሚኮ) በመጪው ክረምት ለ50 ሺህ መምህራን እና የትምህርት አመራሮች የብቃት ሥልጠና እንደሚሰጥ የትምህርት ሚኒስቴር ገልጿል። ሥልጠናው የትምህርት ጥራት ችግርን ለመቅረፍ እና የመምህራንን ብቃት ለማሳደግ ያለመ ሲኾን በተመረጡ ዩኒቨርሲቲዎች እና ኮሌጆች ይሰጣል ነው የተባለው።
በትምህርት ሚኒስቴር የመምህራን እና የትምህርት አመራር መሪ ሥራ አሥፈጻሚ ሙሉቀን ንጋቱ (ዶ.ር) መምህራኑ የሚሰለጥኑት በሚያስተምሩት ትምህርት እና በማስተማሪያ ዘዴዎች ዙሪያ መኾኑን ተናግረዋል። ለ42 ሺህ መምህራን 120 ሰዓት፤ ለ8 ሺህ የትምህርት አመራሮች ደግሞ የ60 ሰዓት ሥልጠና እንደሚሰጣቸው ነው የተገለጸው፡፡ ሥልጠናውን ሲያጠናቅቁም ፈተና እንደሚወስዱ ነው ሥራ አሥፈጻሚው የተናገሩት፡፡
ሥልጠናው በመምህራን እና የትምህርት አመራሩ ላይ ያለውን የማስተማር ዘዴ እና የዕውቀት ክፍተት ለመሙላት እንደሚያግዝ ታምኖበታል፡፡
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!