
ባሕር ዳር: ሚያዚያ 14/2016 ዓ.ም (አሚኮ) በደቡብ ወሎ ዞን የሚገኘው የሰሜን ምሥራቅ ዕዝ አመራሮች ከዞኑ የፀጥታ ዘርፍ ኀላፊዎች እና ከዞን አሥተዳዳሪዎች ጋር በሰላም እና በፀጥታ ጉዳዮች ዙሪያ ተወያይተዋል። በውይይቱ ላይ የተገኙት የሰሜን ምሥራቅ ዕዝ ዋና አዛዥ ሌተናል ጄኔራል አሰፋ ቸኮል ኮሩ ከፀጥታ ኃይሎች ጋር በጥምረት በሠራቸው ሥራዎች ተደራራቢ ድሎች መመዝገባቸውን ገልዋል።
ቀጣይም በጥምረት የሰላም ግንባታ ሥራዎችን እና ቀሪ ተልዕኮዎችን በአግባቡ በመፈጸም ውጤት እናመጣለን ነው ያሉት። የደቡብ ወሎ ዞን አሥተዳዳሪ አሊ መኮንን የዕዙ ሠራዊት በከተማው ሰርጎ ገቦችን በመቆጣጠር እና ይዞ ለሕግ በማቅረብ ረገድ በርካታ የሠላም ሥራዎች እያከናወኑ መኾኑን ገልጸዋል። የሕዝቡን ሠላም ሙሉ በሙሉ ለማረጋገጥ አሁንም ቀሪ ሥራዎች እንዳሉም ጠቁመዋል።
የደሴ ከተማ አሥተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ሳሙኤል ሞላልኝ መከለከያ ሠራዊቱ ለማንም ፖለቲካ የማይወግን፣ ለሕዝብ እና ለሀገር የቆመ ታማኝ ሠራዊት በመኾኑ ማገዝ እና አብሮ መሥራት እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል። ሠራዊቱ ምስጋና ይገባዋልም ማለታቸውንም ከመከላከያ ሰራዊት ማኅበራዊ ትስስር ገጽ የተገኘ መረጃ ያመላክታል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!