
ባሕር ዳር: ሚያዝያ 10/2016 ዓ.ም (አሚኮ) የክፍለ ጦሩ አዛዥ ኮሎኔል ይመር ገበየሁ እንደገለጹት በደቡብ ሜጫ ወረዳ ገርጨጭ በተሰማሩት የሁለት ክፍለ ጦር የተለያዩ ሬጅመንቶች በ60 የጽንፈኛዉ ቡድን አባላት ላይ የማያዳግም እርምጃ ሲወስድ 80 መቁሰላቸውን አስታውቋል፡፡
አዛዡ አክለዉም በሪም፣ በብራቃት፣ በመርዓዊ፣ በአዴት የተሰማሩት እነዚሁ የሠራዊት አሀዶች እና የአማራ ክልል የፀጥታ ኃይል የተጋረጠባቸውን ሰው ሠራሽ መሰናክል እያስወገዱ ጽንፈኛውን የማጽዳት ግዳጃቸውን በብቃት መወጣታቸውን ገልጸዋል፡፡ የዚህ ክፍለ ጦር አራተኛ ሬጅመንት በበኩሉ ከመርዓዊ ተነስቶ ሪም፣ ከሪም ተነስቶ በአብሮ መኖር አቅጣጫ የጽንፈኛውን ዱካ በማሰስ የሕግ ማስከበር ግዳጁን መፈጸሙ ገልጿል።
ሠራዊቱ በቆጋ፣ በቂም ተራራ፣ በእናሸንፋለን፣ በጎጨው እና በሌሎችም ቀበሌዎች ተሰማርቶ ሰላም በማምጣት ለልማት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ኮሎኔል ይመር አስረድተዋል። ሁለተኛ ሻለቃ በዱር ቤቴ አንደኛ ሻለቃ ደግሞ በሊበን የተሰጣቸውን ግዳጅ በተገቢው እየተዋጡ እንዳሉም ተናግረዋል።
ሠራዊቱ በደረሠባቸው አካባቢዎች ያሉ የኅብረተሰብ ክፍሎች በተገኘው ሰላም የአፈር ማዳበሪያ በመውሰዳቸዉ መደሰታቸውን እና ከሠራዊቱ ጎን እንደሚቆሙም ተናግረዋል።
መረጃው፡- የጎጃም ኮማንድ ፖስት ነው፡፡
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!