
ባሕር ዳር፡ መጋቢት 16/2016 ዓ.ም (አሚኮ) በፌደሬሽን ምክር ቤት አፈጉባዔ አገኘሁ ተሻገር የተመራ የኢትዮጵያ የልዑካን ቡድን በ148ኛው የዓለም ፓርላማዎች ኅብረት ጉባዔ ላይ እየተሳተፈ ይገኛል። 148ኛው የኅብረቱ ጉባኤ “የፓርላማ ዲፕሎማሲ፡ ለሰላምና መግባባት ድልድይ መገንባት” በሚል መሪ ቃል በስዊዘርላንድ ጄኔቫ ከተማ እ.ኤ.አ ከመጋቢት 23 እስከ 27 ቀን 2024 ድረስ በመካሄድ ላይ ይገኛል።
አፈጉባዔ አገኘሁ ተሻገር በትናንትናው ዕለት በተካሄደው የጉባዔው መክፈቻ ላይ ንግግር ማድረጋቸው ተገልጿል። አፈ ጉባኤው በሩሲያ ሞስኮ በሙዚቃ ኮንሰርት ተሳታፊዎች ላይ በደረሰው የሽብር ጥቃት የተሰማቸውን ጥልቅ ሃዘን በራሳቸውና በልዑካን ቡድኑ ስም ገልፀዋል።
በዓለም ላይ የሚታየውን የሰላምና ፀጥታ ችግር ለመቅረፍ የፓርላማ አባላት የበኩላቸውን አስተዋፅኦ ለማበርከት እንዲችሉ ጉባዔው በወሳኝ ወቅት መካሄዱ ልዩ ያደርገዋል ሲሉ አፈጉባዔ አገኘሁ በመድረኩ ተናግረዋል። በጉባዔው የፓርላማ አባላት በቀጣይ ቀናት በሚኖራቸዉ ውይይት፤ በዓለም ላይ ሰላምና መረጋጋት ለማምጣት የሚያስችሉ ሀሳቦች ላይ የተሻለ ግንዛቤ እንዲጨብጡ ጥሩ ዕድል ይፈጥራል ብለዋል።
በተጨማሪም በአፍሪካ፣ በመካከለኛዉ ምስራቅ ፣ በዩክሬን እና በሌሎች የዓለም ክፍሎች የሚካሄዱ የተለያዩ ግጭቶችንና ጦርነቶችን ለማስቆም፤ ከፓለቲካዊ ቁርጠኝነት በተጨማሪ የፓርላማ አባላት ተሳትፎ በእጅጉ ያስፈልጋል ነው ያሉት።
ኢትዮጵያ በዓለሞ ላይ ሰላምና ፀጥታን ለማምጣት በከፍተኛ ቁርጠኝነት እየሰራች መሆኗን ጠቅሰው፤ በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል ተከሰቶ የነበረውን ግጭት መንግሥት በፕሪቶሪያው ስምምነት መሰረት ለመቋጨት እየሠራ መሆኑን ገልፀዋል።
በምስራቅ አፍሪካ ዘላቂ ሰላምና መረጋጋትን ለመፍጠር ቀጣናውን በኢኮኖሚ ማስተሳሰር ወሳኝ መሆኑን በማስታወስ፤ ኢትዮጵያ በቀጠናው ይህንን ለመፍጠር የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታን ጨምሮ የተለያዩ ወሳኝ ሥራዎችን እየሠራች መሆኑን አብራርተዋል።
በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት ለመፍጠር ሀገራዊ የምክክር መድረክ ማመቻቸትን ጨምሮ ሁሉንም ባለድርሻ አካላት ያካተቱ በርካታ ውይይቶች በመካሄድ ላይ መሆናቸውን አፈጉባዔ አገኘሁ ተናግረዋል።
አፈ ጉባኤው በሩሲያ ፌደሬሽን በተዘጋጀው በብሪክስ አባል አገራት አፈ ጉባዔዎች መድረክ ላይ በመሳተፍ፤ የአባል አገራት የፓርላማ ኅብረት በሚጠናከርበት ሁኔታ ላይ ኢትዮጵያ የበኩሏን ተሳትፎ እንደምታደርግ አረጋግጠዋል።
በፈጉባዔ አገኘሁ ተሻገር በተመራው የኢትዮጵያ የልዑካን ቡድን ውስጥ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጂጌ እና ሌሎች የፌደሬሽን ምክር ቤትና የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አመራሮች ፣እንዲሁም በጄኔቫ የኢዲፌዲሪ ቋሚ ተጠሪ አምባሳደር ፀጋአብ ከበበውን ጨምሮ ሌሎች የሚመለከታቸው አባላት መካተታቸውን ከምክር ቤቱ ያገኘነው መረጃ ያመልክታል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!