
ባሕር ዳር: መጋቢት 15/2016 ዓ.ም (አሚኮ) ሁላችንም በምንችለው ሁሉ የአዕምሮ ዕድገት ውስንነት ያለባቸው ወገኖችን በተመለከተ መሥራት እንደሚገባ የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ሣኅለወርቅ ዘውዴ ገልጸዋል፡፡
ዓለም አቀፉ የአዕምሮ ዕድገት ውስንነት ቀን እና “መጋቢትን ከዲቦራ ጋር” መርሐ-ግብር በወዳጅነት አደባባይ ተከብሯል። ፕሬዚዳንት ሣኅለወርቅ በዚሁ ወቅት ባደረጉት ንግግር ሁላችንም በምንችለው ሁሉ የአዕምሮ ዕድገት ውስንነት ያለባቸው ልጆች ላይ መሥራት አለብን ሲሉ አስገንዝበዋል፡፡
ዲቦራ ፋውንዴሽን ተስፋ ነው የሰጠን ያሉት ፕሬዚዳንቷ፤ የአዕምሮ ዕድገት ውስንነት ያለባቸውን ከደገፍናቸው እና እድሉን ከሰጠናቸው ነገ የሀገር ተስፋ መኾን ይችላሉ ብለዋል።
የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ (ዶ.ር) በበኩላቸው የአዕምሮ ዕድገት ውስንነት ያለባቸው ወገኖችን እኩል ተሳታፊ እና ተጠቃሚ ለማድረግ ጉዳዩ በአካል ጉዳተኞች ሕግ ላይ እንዲገባ መደረጉን አስታውቀዋል፡፡
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!