
የክፍለጦሩ አዛዥ ሌተና ኮሎኔል አዱኛ ማሞ እንደተናገሩት ክፍለ ጦሩ ከአማራ ክልል የፀጥታ ኀይል ጋር በጋራ በመሆን ባለፉት ሰባት ወራት በምሥራቅ ጎጃም ዞን የተለያዩ የግዳጅ ቀጣናዎች በመሠማራት የሕዝብ ሰላም ሲነሳ የነበረው ጽንፈኛ ቡድን ላይ ተገቢዉን ሕግ የማስከበር እርምጃ እየወሰደ መሆኑን አስታዉቋል።
በሰኞ ገበያ፣ በመርጦለማርያም፣ በግንደወይኒ፣ በእነብሴ ሳር ምድርና ጎንቻ ወረዳ ያደረገው ስምሪት የሠራዊቱና የአማራ ክልል የፀጥታ ኀይል ጀግንነት የታየበት እና የጽንፈኛውን ቅስም የሰበረ መሆኑን አረጋግጠዋል። ሌተና ኮሎኔል አዱኛ እንዳሉት፣ ክፍለ ጦሩ በጎጃም ስምሪት ከጀመረበት ነሐሴ 2015 አንስቶ 456 ጽንፈኞችን ሲደመሰስ 674 አቁስሏል፤ 41 ማርኳል።
በኦፕሬሽኖቹ 60 ኤ ኬ ኤም፣ አንድ ፒ ኬ ኤም/መትረየስ፣ 12 ሽጉጥ፣ 47 የተለያዩ የነፍስ ወከፍ መሳሪያዎች፣ 3 ሺ 110 የኤ ኬ ኤም ጥይት እና ሌሎች ጥይቶችና ወታደራዊ ትጥቆችም ተማርከዋል ብለዋል። ጽንፈኛው ከሕዝብ ዘርፎ የወሰዳቸው ሦስት ፓትሮል፣ አራት ሎንግቤዝ፣ ሦስት ሞተርሳይክል፣ ሁለት ባጃጅ፣ አንድ ኦባማ አይሱዙ በቁጥጥር ስር መዋላቸውንም ጨምረው ዘርዝረዋል።
ሌተና ኮሎኔል አዱኛ እንዳሉት፣ ክፍለ ጦሩ እና የአማራ ክልል የፀጥታ ኀይል በተወጡት እልህ አስጨራሽ እና ውስብስብ ግዳጅ ሕዝቡ ሲፈልግ የነበረውን ሰላም ማስገኘት ችለዋል። በቀጣይም የሕግ ማስከበሩን ስራ የሕዝቡ ሰላም እስከሚረጋገጥ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል። መረጃዉ የጎጃም ኮማንድ ፖስት ነዉ።