
ባሕር ዳር: መጋቢት 04/2016 ዓ.ም (አሚኮ) የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በኢትዮጵያ ከፓኪስታን አምባሳደር አቲፍ ሸሪፍ ጋር ተወያይቷል።
ውይይቱ ኢትዮጵያ እና ፓኪስታን ረጅም ዕድሜ ያስቆጠረ ግንኙነታቸውን ማጠናከር በሚችሉባቸው መንገዶች ላይ ያተኮረ ነው።
የፓኪስታን አምባሳደር አቲፍ ሸሪፍ ሁለቱ ሀገራት በንግድ፣ በቱሪዝም፣ በትምህርት፣ በቢዝነስና በሌሎች ዘርፎች ያላቸውን መልካም ግንኙነት ማጠናከር ያስፈልጋል ብለዋል።የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ፓኪስታን ካራቺ በሳምንት አራት ጊዜ የሚያደርገው በረራ የሀገራቱን ግንኙነት ይበልጥ እንዳሳደገውም ጠቅሰዋል።
የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ዲማ ነገዎ (ዶ.ር) በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ ከፓኪስታን ጋር ያላትን ወዳጅነት የበለጠ የማጠናከር ፍላጐት እንዳላት ተናግረዋል።ኢቢሲ እንደዘገበው የሁለቱ ሀገራት ፓርላማዎችም በጋራ በመሥራት የሕዝብ ለሕዝብ ትስስር መፍጠር ይጠበቅባቸዋል ብለዋል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!