
ደባርቅ: መጋቢት 02/2016 ዓ.ም (አሚኮ) የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት በሰሜን ጎንደር ዞን ሦስት ወረዳዎችን የሚያገናኝውን ከበለስ መካነብርሃን የሚገነባ መንገድን ተመልክተዋል።
የመንገዱ አካል የኾነው 160 ሜትር ርዝመት ያለው የበለገዝ ወንዝ ድልድይ ግንባታ የጉብኝታቸው አካል መኾኑን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል ወይዘሮ አምሳል መንግሥቱ ገልጸዋል።
መንገዱ የእናቶችን እና የአረጋዊያንን የህክምናም ኾነ ሌሎች ማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎችን ይገድብ እንደነበር ነው የምክር ቤት አባሏ የገለጹት፡፡
ይህ መንገድ አሁን ላይ ያለምንም መቆራረጥ እየተሠራ ያለው የአካባቢው ሕዝብ ሰላሙን በአግባቡ በመጠበቅ እና ተቋራጩ ያለምንም ስጋት ሥራ ላይ በመኾኑ እንደኾነ ተገልጿል፡፡
የድልድዩ ግንባታ በርካታ ችግሮችን የሚፈታ መኾኑን በጉብኝቱ የተገኙ የአካባቢው የማኅበረሰብ ክፍሎች ገልጸዋል።
በጉብኝቱ በዞኑ የጃናሞራ፣ የደባርቅ፣ የአዲአርቃይ፣ የጠገዴ፣ የበየዳ እና ጠለምት የሕዝብ እንደራሴዎች፣ የዞኑ ከፍተኛ አመራሮች፣ የመከላከያ ኮንስትራክሽን አመራሮች ተገኝተዋል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!