
ደብረ ብርሃን: የካቲት 29/2016 ዓ.ም (አሚኮ) በዓለም አቀፍ ደረጃ በሴቶች ላይ ከሚከሰቱ የካንሰር አይነቶች የማህጸን በር ጫፍ ካንሰር በቀዳሚነት ይጠቀሳል።
ይህንን አስከፊ በሽታ ለመከላከል በሀገር እና በክልል አቀፍ ደረጃ የቅድመ መከላከል ክትባት እየተሰጠ ይገኛል።
በደብረ ብርሃን ከተማ አሥተዳደርም እድሜያቸው 14 ዓመት የሞላቸው ከ3ሺህ በላይ ልጃገረዶች የማህጸን በር ጫፍ ካንሰር ክትባት እየወሰዱ መኾኑን የከተማው ጤና መምሪያ አስታውቋል፡፡
በመምሪያው የሕጻናት ጤናና ሥርዓተ ምግብ ባለሙያ ናደው ወንድምአገኘሁ እንደገለጹት በከተማው 54 ትምህርት ቤቶች እድሜያቸው ከ9 ዓመት እስከ 14 ዓመት የኾኑ ከ11 ሺህ በላይ ልጃገረዶችን ለመከተብ ታቅዶ ሲሠራ ቆይቷል፡፡
ይሁን እንጅ ካጋጠመ የክትባት እጥረት አንጻር 3ሺህ 73 የሚኾኑት ክትባቱን እንደሚወስዱ አስረድተዋል፡፡በደብረ ብርሃን ከተማም ክትባቱ ከየካቲት 26/2016 ዓ.ም እስከ የካቲት 30/2016 ዓ.ም ድረስ እየተሰጠ እንደኾነም ነው ያስገነዘቡት።
ዘጋቢ፡- ፋንታነሽ መሐመድ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!