
አዲስ አበባ: የካቲት 21/2016 ዓ.ም (አሚኮ) የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ከዋልታ ሚዲያና ኮሙዩኒኬሽን ኮርፖሬት ጋር በመተባበር ያዘጋጁት “የሁለት ውኃዎች ዐቢይ ስትራቴጂ” የተሰኘ መጽሐፍ የምርቃት ሥነ-ሥርዓት እየተካሄደ ይገኛል።
መጽሐፉ ለኢትዮጵያ ሕልውና ከፍተኛ ሚና ባላቸው የዓባይ ወንዝ እና ቀይ ባሕር ላይ የሚያጠነጥን ሲኾን በስድስት ምዕራፎችም የተከፋፈለ ነው።መጽሐፉ የዓባይ ተፋሰስ እና የባሕር በር ጉዳይ ዐቢይ ስትራቴጂ አዲስ ዕይታ፣ በዓባይ ተፋሰስ የውኃ ተጠቃሚነት ጉልህ ሚና መጫወት፣ የሕግና የፖሊሲ ጉዳዮች እንዲኹም ስለ ባሕር በር የዓለም አቀፍ ሕግ፣ የሀገራት ተሞክሮ እና የባሕር በር ታሪካችን በስፋት ተዳስሰውበታል።
የሁለት ውኃዎች ዐቢይ ስትራቴጂ መፅሐፍ በሁለቱ የውኃ አካላት ላይ ጥቅሞቻችን፣ ልንከተላቸው የሚገቡ መርኾች እና ስትራቴጂዎችም ተካትተውበታል።በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የመንግሥት የሥራ ኀላፊዎች፣ የመከላከያ ሠራዊት አባላት፣ ጋዜጠኞች እንዲኹም ታዋቂ ግለሰቦች ተገኝተዋል።
ዘጋቢ:- ራሔል ደምሰው
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!