
ሰቆጣ: ጥር 23/2016 ዓ.ም (አሚኮ)”ሰላም ለሁሉም ሁሉም ለሰላም” በሚል መሪ መልእክት በሰቆጣ ዙርያ ወረዳ በየደረጃው ለሚገኙ የጸጥታ አካላት የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና እየተሰጠ ነው።
በሥልጠናው የሚሳተፉ የጸጥታ አካላትም “የሀገራችንን ታሪክ እና የሰላምን ዋጋ እንድናውቅ የሚያግዝ ትምህርት እያገኘን ነው” ሲሉ አስተያየታቸውን ለአሚኮ ሰጥተዋል።
ዋና ሳጅን በላይ ደርበው ሥልጠናው የሀገርን ሰላም ለማስጠበቅ እና የበለጠ ለመሥራት እንደሚያግዝ ተናግረዋል።
የሚሊሻ አባል የኾኑት ብርሃኑ ታደለ በበኩላቸው “የሀገራችንን እድገት የምናስቀጥለው በአፈሙዝ ሳይኾን በልማት ነው” ብለዋል። ሥልጠናው በቀጣይ የተዛቡ ትርክቶችን እና እውነተኛ መረጃዎችን ለመረዳት የሚያግዝ እንደኾነ ገልጸዋል።
ሥልጠናውን የሚሰጡት ወይዘሮ የሽ ካሴ ሠልጣኞች ለሰላም ግንባታው የበኩላቸውን ሚና እንዲወጡ የሚያደርግ ሠልጠና እንደኾነ ገልጸዋል።ከዚህ ሥልጠና መጠናቀቅ በኋላም ሠልጣኞች በቁርጠኝነት የሀገራቸውን ሰላም በማስጠበቅ ለልማታዊ እንቅስቃሴው የበኩላቸውን አሻራ እንዲጥሉ የሚያደርግ ነው ብለዋል።ሥልጠናው ለተከታታይ 10 ቀናት የሚቆይ እንደኾነ ለማወቅ ተችሏል፡፡
ዘጋቢ፡- ደጀን ታምሩ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!