
ደብረ ማርቆስ: ጥር 22/2016 ዓ.ም (አሚኮ) በምሥራቅ ጎጃም ዞን በአዋበል ወረዳ እና በሉማሜ ከተማ አሥተዳደር የሕዝቡን ሰላም ለመመለስ በሚያስችል ጉዳይ ላይ ለጸጥታ ኃይሉ ሥልጠና እየተሰጠ ነው።
የምሥራቅ ጎጃም ዞን ዋና አሥተዳዳሪ ኑርልኝ ብርሐኑ የጸጥታ ኃይሉ የሚሰጠውን ሥልጠና በሚገባ ወስዶ የዜጎችን ሰላም የመጠበቅ እና የሕግ የበላይነትን ማረጋገጥ ቀዳሚ ተልኮው መኾኑን አስገንዝበዋል።
የምሥራቅ ጎጃም ዞን ኮማንድ ፖስት ሠብሣቢ እና የምዕራብ ዕዝ የ403ኛ ኮር አዛዥ ብርጋዴር ጄኔራል አዘዘው መኮንን የጸጥታ ኃይሉ በተጠናከረ አደረጃጀት የሕዝቡን ሰላም ማረጋገጥ አለበት ብለዋል፡፡ የመከላከያ ኃይልም ድጋፍ መስጠቱን ይቀጥላል ነው ያሉት።
የአዋበል ወረዳ ዋና አሥተዳዳሪ ይኸነው መሥፍን ወረዳው ወደነበረበት ሰላም ተመልሶ የተጀመሩ ልማቶች እንዲቀጥሉ የጸጥታ አካላትን አቅም ማሳደግ እና ሕዝቡ የሰላም ባለቤት እንዲኾን የተጠናከረ ሥራ እየተሠራ መኾኑን ገልጸዋል።
ሠልጣኝ የጸጥታ አካላትም የተዛባ አስተሳሰብን በሥልጠና በማስተካከል የሕግ ማስከበር ተግባራቸውን እንደሚወጡ ተናግረዋል።
ዘጋቢ፡- የኔነህ ዓለሙ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!