
ባሕርዳር: ታኅሳሥ 28/2016 ዓ.ም (አሚኮ) ከአፍሪካ ኢትዮጵያን ጨምሮ ኤርትራ እና ግብጽ የኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓልን ዛሬ እያከበሩ የሚገኙ ሀገራት ናቸው፡፡
እነዚህ ሀገራት የልደት በዓልን በየዓመቱ ታኅሣሥ 29 እና በአራት ዓመት አንድ ጊዜ ደግሞ ታኅሣሥ 28 ነው የሚያከብሩት፡፡
በሩስያ፣ ሰርቢያ፣ ቤላሩስ፣ ሞንቴኔግሮ፣ ካዛኪስታን፣ እስራኤል፣ ቡልጋሪያ፣ መቄዶኒያ፣ ጆርጂያ እና ሞልዶቫም የኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል ዛሬ በታላቅ ድምቀት እየተከበረ ይገኛል፡፡
የሩስያው ፕሬዝደንት ቭላድሚር ፑቲን የዘንድሮውን የኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓልን ሴይንት ፒተርስበርግ በሚገኘው የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስትያን ውስጥ ተገኝተው ማክበራቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ቤላሩሲያውያንም ዕለቱን ቂጣና ዓሣ በማዘጋጀት አክብረውታል፡፡ በሞንቴንግሮ ደግሞ የመልካም ዕድል መገለጫቸው የሆነውን ድፎ ዳቦ በማዘጋጀት እና ስጦታ በመለዋወጥ እያከበሩት ይገኛሉ፡፡
ሰርቢያ ውስጥም ከጫካ ተቆርጦ የተሰበሰበን እንጨት በማቃጠል እና በዙሪያው ተሰባስበው እራት በመብላት የኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓልን እያከበሩ ነው።
ጆርጂያውያን ደግሞ ወደ አውራ ጎዳናዎች በመውጣት የኢየሱስ ክርስቶስን ልደት በመዘከር ላይ ናቸው፡፡
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!