በተለያዩ ምክንያቶች በእሥር ላይ የሚገኙ ግለሰቦች ክስ እንዲቋረጥ መንግሥት ወሰነ።

186

በተለያዩ ምክንያቶች በእሥር ላይ የሚገኙ ግለሰቦች ክስ እንዲቋረጥ መንግሥት መወሰኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ፕረስ ሴክሬታሪ ኃላፊ ንጉሱ ጥላሁን አስታውቀዋል።

በሀገሪቱ የሰው ህይወት መጥፋት፣ ግጭት፣ መፈናቀል እና የሀይማኖት ተቋማት ላይ ጥቃት መከሰቱን ያወሱት የጽህፈት ቤት ኃላፊው በእነዚህ ሁኔታዎች መረጃ የተገኘባቸው 1 ሺህ 682 ሰዎች በቁጥጥር ሥር ሆነው ጉዳያቸው እየታየ መሆኑን አስታውቀዋል።

ከሙስናና በህገ ወጥ መንገድ ከማዘዋወር ጋር በተያያዘ ደግሞ 470 ሚሊዮን 6 መቶ ሺህ ብር ታግዶ ጉዳዩ እየታየ እንደሆነም ነው የገለጹት።

ይሁን እንጂ በታጋሽነት እና የፖለቲካ ምኅዳሩን ለማስፋት ሲል የተወሰኑት ክስ እንዲቋረጥ መንግሥት መወሰኑን ነው አቶ ንጉሱ የተናገሩት። በዚህም መሠረት የ60 ሰዎች ክስ ማቋረጡን ገልጸዋል።

ክሳቸው የተቋረጠላቸው በየትኛው አግባብ፣ በምን ሁኔታ፣ እነማን እንደሆኑ እና ሌሎች ዝርዝር ጉዳዮችን በተመለከተ ጠቅላይ ዐቃቤ ህግ ነገ ማብራሪያ እንደሚሰጥም አስታውቀዋል።

በለውጡ ሂደት ብቻ 43 ሺህ 531 ዜጎች ምሕረት እንደተደረገላቸውም አቶ ንጉሱ አስታውሰዋል።

ፎቶ፦ ከፋይል

Previous articleወልዲያ በሚካሄደው ክልል አቀፍ የስፖርት ውድድር ላይ ዋንጫ ለማንሳት የሚያስችል ዝግጅት ማድረጉን የኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳድር አስታወቀ፡፡
Next articleክሳቸው ከተቋረጠላቸው መካከል ከሰኔ 15 ክስተት እና ከሜቴክ ሙስና ጋር በተያያዘ በቁጥጥር ሥር ከነበሩት ይገኙበታል፡፡