
ባሕር ዳር: ታኅሣሥ 22/2016 ዓ.ም (አሚኮ)ከምግብ እና ሥርዓተ ምግብ ጋር በተያያዘ በዜጎች ላይ የሚከሰቱ ችግሮችን ገና ያልተሻገርናቸው ትልቅ ስብራት መኾኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ገልጸዋል።
አቶ ደመቀ መኮንን በተገኙበት የሰቆጣ ቃል ኪዳን የ2015 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም፣ የ2016 ዓ.ም እቅድ ማጸደቂያና የምግብ ሥርዓት ትራንስፎርሜሽን ማስተዋወቂያ መድረክ እየተካሄደ ይገኛል።
በመድረኩ ባስተላለፉት መልዕክት እንዳሉት በምግብ እና ሥርዓተ ምግብ እድገት ኢትዮጵያ በዓለም ላይ ያላት ደረጃ ዝቅተኛ ነው። በመኾኑም ከምግብ እና ሥርዓተ ምግብ ጋር የተገናኙ ችግሮችን መቅርፍ ለበርካታ ተግዳሮቶች መፍትሔ የሚያመጣ ስለኾነ የሥራ ኀላፊዎች በቁርጠኝነት መሥራት እንዳለባቸው አሳስበዋል።
ኢፕድ እንደዘገበው ስለ ሰው ልማት ስናስብ ማዕከሉ የተመጣጠነ ምግብ ማቅረብ ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያለንን ሀብት፣ ጊዜ እና ዕውቀት አሥተባብረን ከምግብ እና ሥርዓተ ምግብ ጋር ተያይዞ የሚከሰቱ ችግሮችን ለመቅረፍ መረባረብ ይገባል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!