
ባሕር ዳር: ታኅሳሥ 14/2016 ዓ.ም (አሚኮ) ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ጨምሮ የተለያዩ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች የኮይሻ የኀይል ማመንጫ ፕሮጀክትን ጎብኝተዋል፡፡
በአፍሪካ ደረጃ በግዙፍነቱ ሦስተኛ ደረጃ የያዘዉ የኮይሻ ግድብ የንፁህ የኃይል ማመንጨት ሥራ ያለበት ደረጃ አበረታች መኾኑን አመራሮቹ በምልከታቸው አንስተዋል።
በጨበራ ጩርጩራ ብሔራዊ ፓርክ በቅርብ ርቀት የሚገኘዉ የኮይሻ ግድብ ለኢትዮጵያ ተጨማሪ የኢኮኖሚ አቅምና የመልማት ዕድል የሚፈጥር ሲሆን፤ በግንባታ ሂደትም ለበርካቶች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል እየፈጠረ ይገኛል።
በጉብኝቱ ላይ የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንትና የጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ አደም ፋራህ፣ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈጉባኤ ታገሰ ጫፎ፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈጉባኤ አገኘሁ ተሻገር፣ የክልል ርእሳነ መሥተዳድሮች እና ሚኒስትሮች መሳተፋቸውን የደቡብ ምዕራብ ኢትየጵያ ሕዝቦች ክልል የኮሙዩኒኬሽን ቢሮ መረጃ ያመለክታል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!