
ባሕር ዳር: ታኅሣሥ 09/2016 ዓ.ም (አሚኮ) ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን በኢትዮጵያ የሥራ ቆይታቸውን ያጠናቀቁትን የስፔን አምባሳደር ማኑኤል ሳላዛርን በጽሕፈት ቤታቸው ተቀብለው ሽኝት አድርገውላቸዋል።
በውይይቱም ኢትዮጵያ አስቸጋሪ ጊዜያት በገጠሟት ወቅቶች ስፔን ላሰየችው በመርህ ላይ የተመሰረተ እና ወጥነት ያለው አቋም ኢትዮጵያ እውቅና ትሰጣለች ብለዋል።
ኢትዮጵያ ከስፔን ጋር ያላትን ታሪካዊና ሰፊ ትብብር ወደ ስትራቴጂካዊ ደረጃ ለማሳደግ ፍላጎት እንዳላትም ገልጸዋል።
አምባሳደር ማኑኤል ሳላዛር በሥራ ቆይታቸው የሁለቱን እህትማማች ሀገራት ግንኙነት በማስፋት ረገድ ላደረጉት አስተዋፅዖ አመስግነዋቸዋል።
አምባሳደር ማኑኤል በበኩላቸው ስፔን ኢትዮጵያን እንደ ትልቅ አጋር ትቆጥራለች ብለዋል። በልማት ትብብር፣ በንግድ፣ በኢንቨስትመንት፣ በአቪዬሽንና በሌሎችም መስኮች ያለው የሁለትዮሽ ግንኙነት ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በከፍተኛ ደረጃ ጨምሯል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!