
አዲስ አበባ: ታኅሣሥ 06/2016 ዓ.ም (አሚኮ) ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ የበጋ መስኖ ልማትን ለማሳለጥ ከ500 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ አድርጎ 12ሺህ 617 የውኃ መሳቢያ ፓምፖችን ግዥ መፈፀሙን የግብርና ሚኒስትሩ ግርማ አመንቴ (ዶ.ር) ተናግረዋል።
ዛሬ ከአንድ ሺህ 600 በላይ የውኃ መሳቢያ ፓምፕ ለክልሎች ድጋፍ ተደርጓል። እስከዚህ ወር መጨረሻ ሁሉም የውኃ ፓምፖ ወደ ሀገር ውስጥ ገብተው እንደሚሠራጩ ተገልጿል።
ግዥ የተፈፀመባቸው ሁሉም የውኃ መሳቢያ ፓምፖ አሁን ላይ ጅቡቲ መድረሳቸውንም ነው ሚኒስትሩ የገለጹት።
ዘንድሮ ለበጋ መስኖ ልማት የተለየ ትኩረት መሰጠቱን የገለጹት ዶክተር ግርማ፤ ቀደም ብሎ የምርጥ ዘር አቅርቦት እና ማዳበሪያ ወደ ሀገር ውስጥ እንዲገባ ተደርጓል ብለዋል።
በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ባለፉት አምስት ዓመታት ሦስት ሚሊዮን ሄክታር መሬት መሸፈን መቻሉንም ሚኒስትሩ ገልጸዋል።
ዘጋቢ፡- ቤተልሄም ሰለሞን
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
