
አዲስ አበባ: ታኅሳሥ 03/2016 ዓ.ም (አሚኮ) የዜጎችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እና የወጣቶችን የሥራ ዕድል ፈጠራ የሚያግዝ ስምምነት ሁለቱ ተቋማት ተፈራርመዋል ። ስምምነቱ የዲጂታል ኢትዮጵያ ትግበራ አካል እንደኾነ ተገልጿል ።
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከተለያዩ ተቋማት ጋር በሰው ኀይል፣ በቴክኖሎጂ ልማት፣ በሥራ ዕድል፣ በሥራ ፈጠራ፣ በሥራ ላይ ደኅንነት እና በጤና ላይ በጋራ ለመሥራት የሚያስችሉ ስምምነቶችን ከተለያዩ ተቋማት ጋር ስምምነትን በመፈጸም የተለያዩ ተግባራትን በማከናወን ላይ ይገኛል ።
በመኾኑም ዛሬ ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር ቀደም ሲል በጋራ የጀመሯቸውን ሥራዎች ለማጠናከር እና በቀጣይም በአዳዲስ የትብብር መስኮች ላይ በጋራ ለመሥራት የሚያስችላቸውን የስምምነት ሰነድ እንደተፈራረሙ ተገልጿል።
የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈርያት ካሚል በፊርማ ሥነ ሥርዓቱ ስምምነቱ ከዚህ ቀደም ሁለቱ ተቋማት የጀመሯቸውን እና በአዲስ የተግባቡባቸውን ጉዳዮች ወደ ተግባር የሚለውጥ ነው ብለዋል።
የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍሬሕይወት ታምሩ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን በስፋት ለማቅረብ፣ የሥራ ፈጠራን ለማበረታታት እና የዜጎችን ዘላቂ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያስችል ስምምነት ነው ብለዋል።
ዘጋቢ፦ ድልነሳ መንግሥቴ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!