
ጎንደር: ኅዳር 12/2016 ዓ.ም (አሚኮ) የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ የ2016 ሩብ ዓመት ሥራዎችን ገምግሟል። በግምገማው በምዕራብ አማራ ጎንደር ቀጠና በ7 ዞኖች የተከናወኑ የግብርና ሰብል ልማት፣ የችግኝ ተከላ እና እንክብካቤ፣ የግብዓት አቅርቦት እና የደረሡ ሰብሎች ስብሰባ ያለበት ሁኔታ እና ሌሎች ተግባራትን ዳስሷል።
በምክትል ርእሰ መሥተዳድር ማዕረግ የአማራ ክልል የገጠር ልማት አስተባባሪና የግብርና ቢሮ ኀላፊ ድረስ ሳሕሉ ቀዳሚው ተግባር ለልማቱ ወሳኝ የኾነውን በክልሉ ያለውን ሰላም ማረጋገጥ እንደኾነ ተናግረዋል፡፡ በክልሉ ከፀጥታ ሥራው ባለፈ ኅብረተሰቡ የግብርና ሥራው ላይ በትኩረት እንዲሠራ መደገፍ ይገባልም ብለዋል ።
የኅብረተሰቡ ወደ ልማት መዞር ለሰላሙ እገዛ ያደርጋል ያሉት ቢሮ ኀላፊው የደረሱ ሰብሎች በትኩረት እንዲሰበሰቡ ማድረግ እና የመስኖ ሥራ ላይ ማተኮር የቀጣይ የትኩረት አቅጣጫ መኾናቸውን ጠቁመዋል።
በ2015/16 የምርት ዘመን አምስት ሚሊዮን ሄክታር መሬት በመኸር ሰብል ተሸፍኗል። 160 ሚሊዮን ኩንታል ምርትም ይጠበቃል ነው የተባለው።
ለመኸር ሰብል 4 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሩ ተሰራጭቷል፡፡ በክልሉ እስካሁን የተሰበሰበው ሰብል 69 በመቶ እንደኾነም ተገልጿል።
ዘጋቢ፡- ተስፋዬ አይጠገብ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!