
ከ100 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ የተደረገበት የወረታ ደረቅ ወደብ እና ተርሚናል የመጀመሪያ ምዕራፍ ግንባታ ዛሬ ተመረቀ።
የደረቅ ወደብ ግንባታው በሦስት ሄክታር መሬት ላይ ያረፈ ነው፡፡ በአንድ ጊዜ ሳይደራረብ 973 ኮንቴይነሮችን፣ በመደራረብ ደግሞ 1 ሺህ 950 መደበኛ ኮንቴይነሮችን እና ከሦስት ቶን በታች የሆኑ 60 ተሽከርካሪዎችን እንደሚያስተናግድ ተገልጧል።
ወደቡ 75 ቶን ዕቃ መያዝ የሚችል መጋዝን ያለው ነው፡፡
በቀጣይ ምዕራፎች በ20 ሄክታር መሬት ላይ የሚገነባው የወደብ ግንባታ ሙሉ በሙሉ ሲጠናቀቅ በአንድ ጊዜ እስከ 9 ሺህ 450 ኮንቴይነሮችን ያስተናግዳል፤ በዓመት ደግሞ 95 ሺህ 800 ኮንቴይነሮችን የማስተናገድ አቅም ይኖረዋል።
የደረቅ ወደቡ ግንባታው መጋቢት 5 ቀን 2011 ዓ.ም ነበር ወደ ሥራ የገባው።
የደረቅ ወደቡ የመጀመሪያ ዙር ግንባታ በኢትዮጵያ የባሕር ትራንስፖርት እና ሎጀስቲክ አገልግሎት ድርጅት ነው የተገነባው፡፡
ወደቡ የቢሮ፣ መጋዝን፣ ተርሚናል፣ ካፍቴሪያ እና ሌሎች ግንባታዎችን ያካተተ ነው፡፡
ደረቅ ወደቡ በኢትዮጵያ ስምንተኛው መዳረሻ መሆኑም ተገልጧል።
በመርሀ ግብሩ የአማራ ክልል ርእሰ መሥተዳድር ተመሥገን ጥሩነህ፣ የክልሉና የፌዴራል የሥራ ኃላፊዎች እና በሱዳን የገዳሪፍ ክፍለ ግዛት ዋና አስተዳዳሪ የሚመራ ልዑክ ተገኝተዋል።
ትኩስና ተከታታይ መረጃዎችን ለማግኘት በእነዚም አማራጮች ይከታተሉን፡፡
ቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
ትዊተር https://bit.ly/37m6a4m
ዮቱዩብ https://bit.ly/38mpvDC
ዘጋቢ፡- ዳግማዊ ተሠራ- ከወረታ