
ጅግጅጋ: ኅዳር 8/2016 ዓ.ም (አሚኮ)18ኛውን የብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ቀን በሶማሌ ክልል ይከበራል። ለበዓሉ እየተደረገ ያለውን ዝግጅት ለመቃኘት ከተለያዩ የመገናኛ ብዙኀን ተቋማት የተውጣጣ የጋዜጠኞች ቡድን በክልሉ ጉብኝት እያደረገ ነው።
የጋዜጠኞች ቡድን በክልሉ ቀደምት እና ትላልቅ ከተሞች ባደረገው ቅኝት የተረጋጋ እና ሰላማዊ እንቅስቃሴዎችን ተመልክቷል። አስተያየታቸውን ለአሚኮ የሰጡ የጎዴ እና ቀብሪደሃር ከተማ ነዋሪዎች ከዚህ ቀደም የተለያዩ የጸጥታ ችግሮች እና የደህንነት ስጋቶች ነበሩ ብለዋል። በአሁኑ ወቅት ግን የሰላም አየር እየተነፈሱ መኾናቸውን ተናግረዋል።
ነዋሪዎቹ እንደሚሉት አሁን ባለው ኹኔታ ደስተኞች ናቸው፤ ሁሉም ሰው በሰላም እየሠራም እየኖረም ነው።
አስተያየት ሰጪዎቹ በሁሉም የኢትዮጵያ ክፍሎች ሰላም እንዲመጣ እና በነጻነት ሠርቶ ሃብት ማፍራት እንዲቻል መንግሥት እና ሕዝብ መነጋገር እና መደማመጥ ይኖርባቸዋል ብለዋል።
ኢትዮጵያውያን ተከባብረን እና ተዋደን ስንኖር ሰላምና ልማት ይመጣል ብለዋል። ለመጪው የብሔረሰቦች ቀን በዓልም እንግዶች ያለምንም ስጋት ወደ ክልሉ እንዲመጡ ጋብዘዋል።
ዘጋቢ:- ድልነሳ መንግሥቴ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!