
ባሕር ዳር: ኅዳር 4/2016 ዓ.ም (አሚኮ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሐመድ (ዶ.ር) ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በምላሻቸውም ሕብረ ብሔራዊት ኢትዮጵያን መገንባት እንደሚገባ ተናግረዋል፤ ሁልጊዜም አንድ የሆነች ጠንካራ ሀገርን መገንባት እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል፡፡
የጋራ የሆነ፣ የወል የሆነ፣ የማይገፋ እና ሁሉን የሚያቅፍ ትርክት እንገንባም ነው ያሉት፡፡ ታሪክ ሙያዊ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ታሪክ ሁሉም ሰው እኩል አይረዳውም፣ አይጽፈውም አይናገረውም፣ ሙያውን ለሙያተኞች መተው ጠቃሚ ይሆናል ነው ያሉት፡፡
ታሪክን ሙያተኞች ባላቸው እውቀት ቢሠሩት መልካም መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ በኢትዮጵያ ሰማይ ሥር አሁን ላይ አየሩን የያዘው ፖለቲካዊ ታሪክ ብቻ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡
ሌሎች የጋራ ታሪኮችን ማጉላት እንደሚገባ እና በፖለቲካዊ ታሪክ ላይ ብቻ ሌሎችን ታሪኮች መደፍጠጥ እንደማይገባ አንስተዋል፡፡
ሚዛናዊ የሆነ ታሪክን መውሰድ እና በጋራ መትጋት ይገባልም ብለዋል፡፡
ዘጋቢ፦ ታርቆ ክንዴ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
