
ጎንደር: ጥቅምት 30/2016 ዓ.ም (አሚኮ)በማዕከላዊ ጎንደር ዞን የጎንደር ዙሪያ ወረዳ የሀገር ሽማግሌዎች እና የሃይማኖት አባቶችና የሚመለከታቸው አካላት ስለሰላም እና አካባቢው መረጋጋት ዙሪያ ባደረጓቸው ውይይቶች ወጣቶች ወደ ሰላም እየተመለሱ መኾኑን የወረዳው አሥተዳደር አስታውቋል።
የማዕከላዊ ጎንደር ዞን የጎንደር ዙሪያ ወረዳ ዋና አሥተዳዳሪና የኮማንድ ፖስት ሰብሳቢ ኤርሚያስ ቢራራ በወረዳው በሁለት ዙር 92 ወጣቶች ወደ ሰላም መመለሳቸውን ገልጸዋል።
ከአንድ ወር በፊት 41 ወጣቶች ወደ ሰላም መመለሳቸውን የጠቀሱት አቶ ኤርሚያስ አሁን እነዚህ ወጣቶች ተረጋግተው ሥራቸውን ከመከወን ባሻገር ሌሎች ወጣቶች እንዲመለሱም እያደረጉ ይገኛሉ ብለዋል።
በሁለተኛው ዙር ከተመለሱት 51 ወጣቶች ከ20 በላይ የሚኾኑት የተመለሱት በመጀመሪያው ዙር በገቡት ወጣቶች ጥረት መኾኑን አቶ ኤርሚያስ ጠቅሰዋል።
አቶ ኤርሚያስ “ወጣቶች የሰላምን አማራጭ በመከተል ለአካባቢያቸው መረጋጋት እየሠሩ ነው” ብለዋል፡፡
ወደ ሰላም የተመለሱ ወጣቶች የአካባቢያቸውን ሰላም ለማስጠበቅ ጥረት እንደሚያደርጉም አስረድተዋል።
ወጣቶቹ የአማራ ሕዝብ ጥያቄዎች እንዲመለሱ በሰከነ መንገድ ለመወያየትና የጋራ አቋም ለመያዝ የሰላም አማራጭን መምረጣቸውን አስገንዝበዋል፡፡
ዘጋቢ፡- አገኘሁ አበባው
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!