
አዲስ አበባ: ጥቅምት 22/2016 ዓ.ም (አሚኮ)
በአማራ ክልል ተከስቶ የነበረዉ አለመረጋጋት ወደ ሰለማዊ እንቅስቃሴ እየተመለሰ መኾኑን የመንግሥት ኮምዩኒኬሽን አገልግሎት አስታወቀ።
የመንግሥት ኮምዩኒኬሽን አገልግሎት ክልሉን ወደ ሰላም ለመመለስ የተቋቋመዉ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መምሪያ እዝ ያከናወናቸዉን ተግባራት መገምገሙን ገልጿል።
በክልሉ የተፈጠረዉን አለመረጋጋት ለመፍታት በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ሕግ የማስከበር ሥራ መሥራቱን የመንግሥት ኮምዩኒኬሽን ሚኒስትሩ ለገሰ ቱሉ (ዶ.ር) ጠቅሰዋል።
ክልሉ ወደ ሰላማዊ እንቅስቃሴ እንዲመለስ መደረጉንም ነዉ ያነሱት።
በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መምሪያ እዝ በክልሉ በተፈጠረዉ አለመረጋጋት ወደ 3 ሺህ 200 የሚጠጉ ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸዉን ገልጸዋል።
ከእነዚህም ዉስጥ 1 ሺህ 51 ተሃድሶ ተሰጥቷቸዉ ወደ ሰላማዊ አንቅስቃሴ እንዲመለሱ መደረጉንም ነዉ የጠቀሱት።
“የክልሉ ሕዝብ ክልሉ ወደ ሰላም እንዲመለስ የበኩሉን ድርሻ ተወጥቷል” ነዉ ያሉት።
የተጠርጣሪዎች የሰብአዊ መብት አያያዝም ክትትል እየተደረገበት እንደኾነም ገልጸዋል።
ዘጋቢ፡- ኤልሳ ጉዑሽ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!