
አዲስ አበባ: ጥቅምት 12/2016 ዓ.ም (አሚኮ)በሀገራችን ለመጀመሪያ ጊዜ የኾነ የዓለም አቀፍ የሥራ ፈጣሪዎች ሽልማት አዲስ አበባ ሊካሄድ መኾኑን የኢፌዴሪ ሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ገልጿል።
ይህን አስመልክቶ የኢፌዴሪ ሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ሚኒስትር ሙፈሪሀት ካሚል መግለጫ ሰጥተዋል።
በመግለጫቸውም አፍሪካ እንደ አህጉር የወጣቶች መገኛ በመኾኗ ትልቅ ሀብት አላት ያሉ ሲኾን ይህን መልካም ዕድል ጀማሪ ሥራ ፈጣሪዎች በመደገፍ እና ወጣት ሥራ ፈጣሪዎችን ማበረታታት መድረኩ የሚዘጋጅበት ዓላማ እንደኾነ ገልጸዋል።
በመድረኩ ለጀማሪ የአፍሪካ ሥራ ፈጣሪዎች ዕውቅና እንደሚሠጥም ሚኒስትሯ በመግለጫው ጠቁመዋል።
መድረኩን የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር እና የኢኖቬሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር በጋራ በመኾን የሚያዘጋጁት ነው። በነገው ዕለትም የመድረኩ ይፋዊ የማብሰሪያ ፕሮግራም ይካሄዳል።
መድረኩ ለሁለት ተከታታይ ቀናት እንደሚካሄድ ከሚኒስቴር መሥራያ ቤቱ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።
ዘጋቢ፡- ቤቴል መኮንን
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!